Tuesday 31 January 2012

ይድረስለዳኞች፦ዳኛ

የጐንቻው!

ሳር ቅጠሉ፤ ገመድ ተፍተለተለና፤

ሽምቀቅ ማተብ ሆነ፤እምነቱ፤ቀረና፤

በላይን ሰቀሉት፤የላቀውን ጀግና፤

ማነቆ አደባባይ፤የትውልድ ገመና፤

ከጠላት ባዳናት፤በአገሩ፤መዲና፤

ስቅላት ውለታው፤እርግምት ነውና፤

ብርክ መዳህ ጀመርን ነፃነት፤ልመና፤

ያውም ከባዕድ አገር ተሰፍሮ፤በቁና፤

በላይ እምቢ ብሎ አኛ እጅ ሰጠንና፤

እንጠፋፋለን ‘አሳር’፤ እንደገና፤

ይድረስ፤ለአገር ዳኛው፤‘ሕዝቡ በደፈና’፤

ዛሬም ‘ክህደታችን’፤አልተፋቀምና፤

ስንት ‘በላይ’ ሰቅለን እንሰይም ጐዳና።



በዘመነ ንጉሥ፤‘በግርማሜ’፤ሞት፤

አገር ሳይቆጣ፤ሳይተጋ፤ወጣት፤

በዘመነ ‘ደርግም’፤በ‘ሺህዎቹ፤እልቂት’፤

ጥቂቶች፤ሲተጉ፤’መንጋው’ ሲራኮት፤

የባሰ፤ደንቀራ፤ተጋረጠበት፤

‘እናት’ በጓዳዋ፤የልጅ ቁርኝት፤

ዘመነ፤ወያኔ፤መከራ፤ግዞት፤

አገር-ሕዝብ፤የሚያሥር፤በዘር ሰንሰለት።



ሕዝብ የሚያስጨርስ ነፍሰ-በላ፤ዳኛ፤

ለምን አይየቅ፤በአገር አደባባይ፤ችሎት ‘መስቀልኛ’፤

ሁነኛ ሰው ጠፍቶ፤ጠበቃ፤የሚሆን፤ አዋቂ ቁርጠኛ፤

‘እድሜ፤ልክ’ እሥራት፤ ተፈረደ ‘በእኛ’፤

ይድረስ ለአገር ሸንጐ፤ይድረስ ለአገር ዳኛ፤

ለምን ፍትህ አትሰጥ፤ይግባኝ የማይሸረው፤በአሳሪና እስረኛ፤

ብይን አስቆጭተህ፤እጥር ምጥን ያለ፤‘ሰውኛ-አገርኛ’፤

አትደግስም ወይ፤በቀናት፤በወራት፤ወያኔን መሸኛ።


በፍርሃት ማዕበል፤አገር ሲጥለቀለቅ፤

በክህደት፤ጐርፍ ምጣት፤ሰው ከቀየው ሲለቅ፤

እንባ ባዘነበው፤ደም በቋጠረው፤ ሃይቅ፤

በወያኔ አዞዎች፤በቁም ሰው፤ሲጨቅ፤

ገመና እሚሸፍን፤ሱሪ፤የሚያስታጥቅ፤

በአገር ጀግና ሲነጥፍ፤ወንዙ፤ምንጩ፤ሲደርቅ፤

ጓዳ እሚያወላዳ፤ቀሚስም እሚያጠልቅ፤

በአዘቦት፤በጥምቀት፤አድባር ሲሸማቀቅ፤

ቅርጣን የተረፉ፤ቃል፤የጠበቁ፤ሃቅ፤

እውነት ትንፍሽ ያሉ፤ዓለማችን እንዲያውቅ፤

የ’ግርማሜን’ መንፈስ፤የበላይን ሰንደቅ፤

እንቁ የአበሻ፤ልጆች፤የትውልድ ፈርጥ ወርቅ፤

ስማቸው፤አርማቸው፤በአለም የሚደነቅ፤

ማተብ ይሁን አልቦ ካቴናቸው፤ይውለቅ፤

ይድረስ ለአገር ዳኛው፤አፎት፤እንዲታጠቅ፤

አሳሪው ይታሰር፤ክህደቱ፤ይሽምቀቅ።



በአኬልዳም ሽብር፤የተፈረጁት፤

‘ጥፋት’ ባጋለጡ፤እስር ስቅላት፤

አንዷለም፤እሥክንድር፤ጀግናዋ ርዕዮት፤

ዘመኑ፤በቀለ፤ናትናዔል፤አሳምን፤ደግሞም፤ውብሸት፤

ከሺህ ተቆራኝተው፤ስለ ሕዝብ፤ስለ አገር የተሳሰሩት፤

ለዓለም መቀጣጫ፤ንብረት-ነፍስ፤አራጣ፤የሚገብሩት፤

መጋጥ በለመደው፤ ያረጀ ያፈጀ ነቅዝ፤ስርዓት፤

ይድረስ የአገር ዳኛ፤ዋስም ጠበቃ ሁን፤ውጣና ‘ታገት’፤

አበሳችን ይሻር፤ሰይም አደባባይ፤የእምነት የምህረት፤

ሕዝብ ሸንጐ፤ጠርቶ፤የብይን ችሎት፤

ይፍረድ፤ የአገር ዳኛ፤በቀን በወራት፤

ታሳሪ፤አሳሪውን፤እንዲጠይቁት፤

በአገርመስቀልኛ፤እንዲያፋጥጡት።

በእስራትና በቅጣት፤ለሚንገላቱ፤ብርቅ ድንቅ ኢትዮጵያዊያን ድጋፍ፡-
·        በውስብስብ ታሪካችን፤ውድ ሕይዎታቸውን መስዋዕትነት ከፍለው፤እንደ ሰው፤እንደ ዜጋ፤ ሰብዓዊ ክብር፤ጸጋ፤ኩራት፤ማንነት አጐናጽፈውን ያለፍ፤ኢትዮጵያዊያን ቁጥር በጣም ግዙፍ ነ፤ ይኸንን ጀግንነታችውን፤ መስዋዕትነታቸውን በአብዛኛው ስንዘክር ኖረናል።
·        ይሁንና በተለይ፤በዚህ በቅርቡ ‘በኛ ዘመን’ ለጊዜውም ቢሆን ‘ደመ-ከልብ’ያደረግናቸው፤እስኪሚያሰኝ፤ የረሳናቸውና፤የተሰውለትን ዓላማ ችላ ያልነው፤ወይም፤ የሕዝቡ፤ቁጭት፤ የደበዘዘ፤ይመስላል። ኃያው ጀብዱ፤ ሰርተው ያለፉ፤ እህት ወንድሞቻችን፤ ወላጆቻቸው እንባ ሳይታበስ፤ ሃዘናቸውን በውስጣቸው ቀብረው፤ በተስፋ የሚኖሩ ወገኖቻችን በጣም ብዙ ናቸው።
·        አሁንም የወያኔ መንግሥት፤ ስለገመተን፤ስለናቀን፤ በሽብር አሳቦ፤ቁጥር ስፍር የሌላቸውን፤ ወገኖቻችንን፤ ብርቅዬ መሪዎቻችን፤ የላቁ፤ ባለሞያዎቻችንን፤ ጋዜጠኞቻችንን፤በእስራት፤ስቅላት፤ ሲያንገላታ፤ሲያሰቃያቸው፤ከንፈር እየመጠጥን፤በየጓዳው፤ቡና የምናቃርር፤ወሬ፤የምናመንዝክ፤ ሞልተናል።
·        እንደዚህ በቀላሉ፤ ለእውነት፤የቆሙ፤እህት ወንድሞቻችንን አሳልፈን የምንሰጥ ከሆነ፤ፍጹም ነፃነት የማይገባን ሕዝቦች ነን፤ከዚህ በኋላ፤በትውልድም፤በታሪክም፤ተጠያቂዎች፤የለየለት የጠላት፤ድቃላ፤ወያኔ ብቻ ሳይሆን፤ ዝምተኛው፤ ‘ሰማኒያ ሚሊዮን’ ሕዝብ ጭምር ነው።
·        በዚይ የሚገርም የታሪክ አጋጣሚ፤ዘመነኞች፤ ደባ-ድራማ፤ በአደባባይ፤እያቀነባበሩ፤ሲያቀርቡልን፤በቁጣ እንኳ፤ ‘ጠጠር’ የወረወረ፤ወይም አመጹን፤ተቃውሞውን፤ በሥራ ማቆም አድማ የገለፀ’ የለም። ከዚህ በላይ ምን ሊመጣ ነው? መቼ ነው ሕዝብ የሚቆጣው?
·        ከአብራኩ የወጡ፤እህት ወንድሞቹን፤ልጆቹን፤ወላጆቹትን፤ እድሜ ልክ ሲያስሩበት፤ሞት፤ስቅላት፤ሲፈርዱባቸው፤ሳይዋደቅ፤ዝም ብሎ ካዬ፤ የዚህ ዓይነት ሕዝብና አገር፤ወገንም፤ዜጋም መሆን፤የሚያስፍር ነው።                    yegonchaw@yahoo.co.uk

No comments:

Post a Comment