Saturday 29 May 2010

እሳት ቢያንቀላፋ ገለባ ጎበኘው

ወንድሙ መኰንን

የኢትዮጵያው ጠቅላይ ስቃይ መለስ ዜናዊ ከምንጊዜውም በበለጠ የማጭበርበር አክሮባት ሠርተው የኛው አባ ጉልቤ “በእንከን የለሹ” ብሔራዊ ምርጫ “ተቃዋሚውን አፈር ድሜ አስግጬው አሸንፍኩ” ብለውን አቅራሩብን! ዓለም አቀፍ ታዛቢዎችም ከዚህ በፊት አይተው የማያውቁት ትርዒት በዝምታ እንዲመለከቱ ተገደዱ። አሜሪካኖቹ ሳይቀሩ በየኤምባሲአቸው እንዲቀረቀሩ ታዘዙ። እንዲህም አርጎ ምርጫ የለም። አባ ጉልቤ ማንን ከመጤፍ ቆጥረው! በአሁኑ ጊዜ እንኳን ለሌላው እና ለታማኙ ተቃዋሚአቸው ለአቶ ልደቱም አልራሩ። ሁሉንም ጠቀለሉት ጃል! አቶ ልደቱ ትንሽ ተዳፈሩ መሰለኝ። በቴሌቪዥን ክርክሩ ጊዜ ምን ያህል መንጠራራት እንደነበረባቸው አቅማቸውን ባለመገምታቸው ገደብ አለፍ አሉ መሰል። ሊቀ መኳሳቸው ፕሮፌሰር ኤፍሬም ይሰሐቅ መክረኛውን ኃይሌ ገብረሥላሴን ይዘው አንድ ነገር እንዲፈጽሙ ተነግሮአቸዋል። ምን ይታወቃል፣ አቶ ልደቱ አቅማቸውን ካወቁ በኋላ፣ በድርድር ሚኒስቴር ሊሆኑ ይችላሉ። ኢሕአዴግ እንደ እግዚአብሔር መሐሪ ሆኖ የለ? በሌላ በኵል ደግሞ፣ በረከት ስምኦን ጋር ፎቶአቸውን እንደባንዲራ እያውለበለቡ፣ ከአብዛኛው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር ያላተሙአቸውንም እንጂኒየሩም ሳይቀሩ በዘሮ ዘረሩአቸው። አሁን እንጂነየሩ እንደተቀየሙ እንዳይቀሩ፣ ምናልባት ፕሮፌሰር ኤፍሬም አሁንም ተዓምር ሊሠሩ ይችላሉ። ክፍት የአማካሪ ቦታ አለ የሚል ፍንጭ እየሰጡን ነው። እርስ በርስ ያናኮሩትም አንድነት ምንም አልበጀው። ብርቱካን እስር ቤት እንደተዘጋች እንዳትሞት እና የሕዝቡን ቁጣ እንዳታነሳ፣ ምናልባት አሁንም ኤፍርም የሚሠሩት ተአምር ሊኖር ይችላል። አቶ መለስ፣ ዋናውን ተፎካካሪአቸው አቶ ስዬ አብራሀን በዚህኛውም መስክ ያለርህራሔ በባዶ ረቱአቸው፡፡ የሕዝቡን እጅ በግድ ጠምዝዘው 99.4% (0.6ቷ የተገባች) ድምጽ ለወያኔ አስመዝግበዋል። የኢሰፓ/ደርግ ፖሊቲካ ጊዜዋን ጠብቃ በሾርኒ ብቅ አለች አይደል? በወያኔ የብሔራዊ ክደት ባለሟሎች ጥቅም ላይ ዋለች እንደገና? ደርጎች ነብሳችሁ አይማርም። አንድ ተጨማሪ ተንኰል አስተምራችሁ ሄዳችሁ። ሰሎሞን ተካልኝ የተባለ ገንዘብ እየተከፈለው የሚዘፍን የአገራችን የጠጅ ቤት አዝማሪ ቢጤ እበላ ባይ ሰው፣ ስንት ብር ግንባሩ ላይ እንደለጠፉለት አይታወቅም፣ ጋንጩሩን አስቀየሚ መለስ ዜናዊ፣ “ቅንድቡ ያማረለት ቆንጆ፣ ምሑር የምሑራን ቁንጮ” እያለ እንዲዘፍንላቸው ግጥም አቀበሉት። ይኸም አልበቃ ብሎአቸው፣ መስቀል አደባባይ በስሜት ገንፍለው ወጥተው ፈንጭተዋል። ግን የፈነጩት ጥይት ከማይበሳው መስታወት በስተጀርባ ነው። ፈሪ ጨካኝ ነው።
የወያኔ ባለሥልጣናት፣ የአገር ቤቱን ሕዝብ አንዴ በክንዳቸው ካዳሸቁት በኋላ፣ ዓይናቸውን በጨው ሙልጭ አድርገው አጥበው፣ ምንም ሳያፍሩ (ድሮስ ማፈር መች ተፈጥሮባቸው?) ውጭ አገር ተበትኖ ወደሚኖረው ስደተኛ ኢትዮጵያዊ በአንድ ልብ ፊታቸውን አዙረዋል። ቢሳካም ባይሳካም ሁሉንም መሞክራቸው መቸም አይቀርም። አዳሜ፣ እየመጡብህ ነውና ስደተኛ ሁሉ ጥግ ያዝ! ወያኔዎች ያንን የቀልድና የልጆች የዕቅ-ቃ ጨዋታ መሰል ምርጫ ላይ ድል ሲቀናጁ፣ ውጭ አገር የተነሰነሱት አሽክሮቻቸውም ጌቶቻቸውን ለማስደሰት አልተኙም። አማራውን በአሞሌ ጨው እያባባሉ በጠነዛው ጉሮኖአቸው ሊሞጅሩት ሰሞኑን አንድ ዘግጀት ለንዶን ውስጥ ደግሰዋል። ሆዳሞቹ ከርሳቸውን ለመሙላት ይሄዳሉ። ሆድን የሚያክል ክፉ አውሬ! ወጥመዱ ውስጥ የሚገቡላቸው አይታጡም። ኢትዮጵያውያን ግን ለሌላ ዙር ትግል እየተደራጁ ነው።
ከዚህ በፊት “ጥጃ ለጅብ?” በሚል አርዕስት አንድ መልዕክት ሞጫጭሬ ነበር። ካላዩት፣ የሚከተለውን የግሌን ድረ-ገጽ ወይም ብሎግ ይመልከቱ። http://wondimumekonnen.blogspot.com/
በዚያ ርዕስ እንድጽፍ ያኔ ያስገደደኝ ምክንያት በዚያን ሰሞን ወያኔ እንደዛሬው ወጥምድ ጠምዶ ስደተኛውን ሊመዝብር ደርሰንበት ነበር። በጊዜው የለንዶኖች የወያኔ ጥቅም አስጠባቂዎች በኤምባሲው አማካኝነት በአካባቢው ኗሪ ስደተኛውን ኢትዮጵያዊ ሕብረተሰብ በየሬስቶራንቱና በየመጠጥ ቤቱ እያደኑ፣ “አገራችሁ በጣም ተሻሽላለችና፣ ገንዘባችሁን በፓውንድ ኢትዮጵያ ባንኮች ውስጥ አስቀምጡ። ወለድ ይወልድላችሁአል። በፈለጋችሁ ጊዜም ልታወጡት ትችላላችሁ፤” እያሉ በተለመደው የቁጭ-በሉ ታክቲካቸው ሊያታልሉ ስሞክሩ ነበር “ጅብን ጥጃ ጠብቅ ብለው አምነው አይተውለትም” ብዬ ወገኔን ያስጠነቀቅኩበት። ወያኔ የውጭ ምንዛሪ ባገኘው መንገድ ለመመዝበር አስቦ አልሰሜን አባብሎ አስግበቶ ለመሞጭለፍ የነደፈው ታክቲክ ውሀ በላው። አይታሰብም! ወገናችን ነቃ። ዕቅዳቸው ከሸፈ። ጎበዝ!! አሁን ደግሞ ሌላ የባሰ ተንኰል እየመጣብህ ነውና፣ ኢትዮጵያዊ ሁሉ እጂጌህን ሰብስብ። በያለህበት ንቃ! ለወያኔ አትታለል። ለነዚህ የቀን ጅቦች እራስህን አትሰዋ። ኦሮሞን፣ አማራን፣ ወላይታን፣ ሲዳማን፣ ጉራጌን እየነጠሉ፣ በልማት ማኅበር ስም እየከፋፈሉ ዲያስፖራውን ሊያዳክሙ በአጭሩ ታጥቀው ተነስተዋልና ተዘጋጅተን እንጠብቅ። ከዚህ በፊት በፍረንጆቹ አቆጣጠር 2006 ዓመተ ምሕረት ላይ፣ በያለንበት ሊያኮላሹን የነደፉቱትን 52 ገጽ የፈጀ እቅዳቸውን አግኝተን ይፋ አድረግን ነበር። ካላዩት፤ የሚከተለውን ድረ-ግጽ በአስሊ መኪናዎ አመልካች ጠቁመው ያንብቡ።
http://www.ethiomedia.com/carepress/attack_on_diaspora.html
የወያኔ አሽከሮች፣ ያንን ሰነድ ሥራ ላይ ለማዋል ዛሬም ሌት ተቅን ይባዝናሉ። እንቅልፍም አይተኙም። ተኝተውም አያድሩም። ነገር ሲጎነጉኑ ውለው ነገር ሲጎነንጉኑ ያድራሉ። ሰሞኑን በጉያቸው ሸጉጠው ብቅ ብቅ ያሉባት ታክቲክ በጎን ሲታይ አያ ጅቦ ሆዬ ጥጃውን እራሱን “ና! ለምለም ሳር ያለበትን አውቃለሁ። ንጹህ ውሀ የሚፈስበትን ምንጭ አሳይሀለሁ፣ ደግ እረኛህ እኔ ነኝ። ና ላሰማራህ!” የሚል አባባይ ደም የጠማው ተንኰለኛ ተኵላ ይመስላል። ይኸ የወያኔዎቹ እንቅስቃሴ፣ ከወጥመድነቱም ባሻገር፣ አማራው ላይ የወረደ ስድብ ነው። ወያኔ አማራን ሊያደራጅ! ጉድ ነው!
ወያኔ ትላንትና “አማራ ጠላታችን ነው። አማራ ጨቋኝ ነው። አምራ ነፍጠኛ ነው” እንዳላለ፣ አሁን ደግሞ “አማራውን በልማት ማኅበር ላደራጅ” ብሎ “ተቆጣጢርና ደምሲስናውን” ስትራተጂ ነድፎላችሁ በአጭሩ ታጥቆ በድፍረት ተነስቷል። ጅል አማራ-አማራው እየተመረጠ ይጃጃልለት እንዶሆነ እንጂ፣ መቸም በጤናው ስድቡን እየጠጣ ከወያኔ በታኝ ቡድን ጋ በደኅና አዕምሮው የሚተባበር ይኖራል ብዬ አልገምትም። ይኸ አባባሌ ታዲያ ሆድሞችን አይጨምርም። ሒሊና ቢሶችን ቁጥር ውስጥ አይገቡም። ሆዳሞቹማ አይደሉም እስከዛሬ ያስጠቁን? ወያኔዎች እንዲህ የሚል ድብዳቤ ለጥቁር (ተለጣፊ) አማሮች፣ ለአስመሳዮችና እንዲሁ ለየዋሆች ልከዋል!።
“አልማ (አማራ ልማት ማኅበር መሆኑ ነው) 2002 ... በቅርቡ አዲስ አበባ ሚሌኒየም አዳራሽ በተካኼደ የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅት 1.2 ሚሊዮን ብር ገቢ ማሰባሰብ ችሏል።
በዚህም መሰረት በእንግሊዝ አገር አልማ ኮሚቴ ተቋቁሞ እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ ሲሆን፣ እ.ኤ.አ ሜይ 29 ቀን 2010 አቶ ሕላዊ ዮሴፍ የአማራ ልማት ማኅበር (አልማ) የቦርድ ሊ/መንበር በተገኙበት ታላቅ የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጀት ይደረጋል።
ስለሆነም በዚህ ታላቅ ዝግጀት ላይ ተገኝተው የበኩልዎን አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ጥሪአችንን እናቀርባለን።”
“አልማ” አሉት? “አጥፋ” ባሉት ባማረላቸው። “የአማራ ጥፋት ማኅበር”!!! ገሩምና ደግም ልክ ነው። የግብዣ ደብዳቤው ላይ የኢትዮጵያን ኤምባሲ ማኅተም ጉብ ብሎበታል። አምባሳደር ብርሀኑ ጥሩ ግልጋሎት እየሰጡ መሆን አለበት። ቦታውም እዚያው “ኢትዮጵያ ኤምባሲ ነው”። ጃንሆይን ያመስግኑ። ምን የመሰለ የተንጣለለ ቤት ለነዚህ ጉዶች ጥለውላቸው አለፉ። ወያኔዎች አንዴ ቤቱን ሊሸጡት ሲያስማሙ ነበር። ንጉሡ አንድ ያሠሩት ሕግ ነገሩን አፈረሰባቸው መስል መሸጥ አቃታቸው። ጉድ ነው። እንግዲህ በዚሁ አዳራሽ ነው የአማራ ጥፋት ማኅበር ሊደራጅ የተደገሰለት። ወያኔ አማራን ሊያደራጅ!!! ያውም በልማት ማኅበር አደራጅቶ እንደከብት ሊነዳ! እኔ ልንገራችሁ ቁርጡን! ወያኔ ያደራጀው አማራ፣ ዝናብ ያጨቀየው አቧራ!!! የጨቀየ ጭቃ ልብስና ጫማ ከማቆሸሽ ባሻገር ለምን ይጠቅማል? ጭቃን እያነሱ የሆን ነገር ላይ፣ ከመልደፍ፣ ከመደፍደፍ፣ ከመለጠፍ፣ ከመመረግ በስተቀር ምን ይደርግበታል? ከወያኔ የሚተባበር፣ ያው ተለጣፊ ጭቃ አይደል? የጭቃም ጭቃ! አንድ የምወዳቸው አዛውንት አንዴ የሆነ ነገር ግርም ብሎአቸው በአንድ ስብሰባ ላይ፡ “የቸገረው ዱቄት ከነፋስ ይጠጋል” ብለው አስደመሙን። ዱቄቱስ መጠጊያ አጥቶ ነው ከበታኙ የሚጠጋው፣ ስደተኛው አማራ ምን ቸግሮት ነው ከአራጁ ጋር የሚውለው? የወያኔስ ድፍረት አላበገናችሁም? “እሳት ቢያንቀላፋ ገለባ ጎበኘው” ይሉሀል ይኸ ነው። አማራው ያለወትሮው ተኝቶ ሲገዛላቸው የወያኔዎች ድፍረት ድንበሩን ጣሰ። ማፈር ቀረ። መፍራት ቀረ። ጎበዝ አንድ በሉ!!
እስቲ ከድሮው የወያኔ ካድሬ፣ አሁን እራሱን ነጻ ካወጣው፣ ከተስፋዬ ገብረአብ መጽሐፍ ትንሽ እንመልከት። (ነገሩን ያገኘሁት ከ”ደራሲው ማስታወሻ” ተስፋዬና አንዳርጋቸው ካደረጉት ውይይት፣ በ125 ገጽ ላይ ነው)።
“በኢህአዴግ የድርጅት ኮሚቴ ደረጃ ውይይት ከተደረገበት በኋላም፣ ኢሕዴንን ወደ አማራ ድርጅትነት ለመለውጥ ጥናት ይደረግ ተባለ። ጥናቱ “አማራነት ምንድነው?’ ለሚለው ጥያቄ ምላሽ እንዲሰጥ መመሪያ ተሰጠ። ክዚህ በሁዋላ ቀጣዩ ጥያቄ፣ ጥናቱን ማን ይስራው?’ የሚል ነበር።

አንዳርጋቸው ትረካውን አቋርጦ መሳቅ ጀመረ።

ምንድነው የሚያስቅህ?’ አልኩ

‘ጥርናቱን ማን እንዲያካሄድ እንደተወሰነ ታውቃለሁ?’

‘ማን ሆነ?’

‘በረከት ስምኦን”

በረከት እኮ ማለት አማራን በጣም የሚጠላ፣ አማርኛን መናገር የሚጸየፍ፣ የዞረበት ዘረኛ ዜጋ ነው። ለምሳሌ በቪኦኤ ትግርኛው ፕሮግራም ቃለ መጠይቅ በደስታ በትግርኛ ሲሰጥ፣ እንግሊዝኛው ፕሮግራም ላይ ቀርቦ በእንግሊዝኛ ሲንተባተብ፣ በአማርኛው መርሀ ግብር ላይ ግን አማርኛ ላለመናገር ጨርሶ የማይካፈል፣ ጸረ አማራ ስሜት የተጠናወተው ጠብራራ ፍጡር ነው” ሲፈጠር ክፋትና ውሸት አብሮት ተፈጥሮ አብሮት ያደገ ያጨካኖች ቁንጮ ሲሆን፣ ወያኔ በመልኩ የጠፈጠፈው የአማራው፣ ድርጅት መሪ ነው። ምን እሱ ብቻ፣ ተፈራ ዋልዋ የተባለ ዘረኛ፣ አንዲት ጠብታ የአማራ ዘር በማይስክሮስኮ ሥር ቢመረመር የማይገኝበት ፣ (ተስፋዬ ገብረአብና አንዳርጋቸው የጊሚራ ተወላጅ ተወላጅ ነው ይሉታል መጽሐፉ ውስጥ)፣ የአማራውን ድርጅትን ቀፍድዶ ይዞ አመራር ላይ ጉብ ብሎ የወያኔን ጉዳይ ያስፈጽማል። እነዚህ ሁልቱ መርዘኞች ነበሩ፣ ዲላና አዋሳ በተካሄደው ስብሰባ “የኢህአዴግም፣ የደቡብ ሕዝብም ጠላቶች አማራና ጉራጌ ኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች ናቸው” ብለው መርዝ ሊረጩ ሲሞክሩ፣ የወላይታና የሲዳማ ብሔረሰብ አባሎች አዋርደዋቸው የመለሱአቸው። ተፈራ ሲናገር፣ “የአማራ ብሔረስብ አይታመንም። ዝም ብሎ አድፍጦ ጠብቆን በካርዱ አደባየን” ብሎ ስሞታ አሰማ። እስቲ ይታያችሁ፣ እነዚህ አማራ ላይ በቂም በቀል የተመረዙ ነበሩ እንግዲህ የተለጣፊው አማራ ብሔረሰብ ድርጅት መሪዎች የሆኑት። ተወልደና አለምሰገድስ ቢሆኑ ትግሬ ሆነው ሳሉ፣ የአማራው ድርጅት ፈላጭና ቆራጭ ሆነው መሰየማቸው ምን ይባላል?

አንዳርጋቸው ንግግሩን ቀጥሎ ተስፋዬን እንዲህ ይላል መጽሐፉ ውስጥ።
“የአማራ ማንነት በረከት ስምኦን እንዲያጠና ታዘዘ። አያይዞ በረከት ቀጠለ። በረከት ስምኦን ጥናቱን ኣጥንቶ ጨርሶ ይዞ መጣ። የሚደንቅ ጥናት ነበር። ፅሑፉ ገና ሲጀምር አማራውን ያወግዛል። አማራው ሌሎች ብሄርብ-ሄረሶቦችን እንዴት እንደጨቆነ ይተነትናል። የአማራው ነፍጠኛ ሌሎች ላይ አደረሰ የሚለውን በደልም ያብራራል። አማራው ሌሎች ሕዝቦች ላይ ፈጸመ የሚባለውን ግፍ አንድ በአንድ ለቅሞ ጽፎአል። በረከት ይሔን ሁሉ አንብቦ ሲያበቃ፣ ‘አማራነት ምንድነው ለሚለው ጥያቄ ምላሽ እንደሰጠ ተማምኖ ወረቀቱን አጣጠፈ።”
እንግዲህ እንዲህ ዓይነት ዓይኑን ያፈጠጠ፣ ጥርሱን ያገጠጠ ጥላቻ የተፈጸመው አገር ቤት ባሉት አማሮች ላይ ነበር። ያም የሆነው አማራ ነን የሚሉ እንደጉልቻ የተጎለቱ፣ እንደ ጉቶ ግማጅ የተተከሉ ባሉበት መድረክ ነበር። በጠመንጃ አፈሙዝ አስገድደው ኣማራው ስድቡን ጠጥቶ፣ ውርደቱኝ ችሎ አገር ቤት አፍዝ አድንግዝ የደገሙበት ይመስላል። ግን ለንዶን ድረስ በድፍረት መጥተው የአማራ ልማት ድርጅት እናቋቁማለን ብለው ሲወዛወዙ ማየት፣ “እውነትም አማራ ተቀልዶበታል” ያሰኛል።
አማራ ነን እያሉ፣ አማራውን ለመቅበር ጎድጓድ የሚቆፍሩ የወያኔ ቅጥረኛ ኩሊዎች፣ ኦሮሞ ነን እያሉ ለሚበደለው ኦሮሞ መቃብር የሚምሱ ሆዳሞች ሞልተዋል። እዚህም ቤት እዚያም ቤት ሞልተው ተርፈዋል። የወያኔ ዓላማ እነዚህን ሆዳሞችን ተጠቅሞ በዘር ከፋፍሎን ኢትዮጵያን ብትንትኗን ሊያወጣት ነው። የዚህ ወይም የዚያ ብሔር ልማት እያለ ገንዘብ ይሰበስባል። ዳሩ ግን የአማራውም ሆነ የኦሮሞው ሕይወት ግን ከድጡ ወደ ማጡ ሲዘቅጥ እንጂ ሲሻሻል አልታየም። ለሆዳሞቹ፣ አንድ መልዕክት አለኝ። መልዕክቱም ሲወርድ ሲዋረድ ከአባቶቻችን የመጣ ነው። በሱው ልዝጋው ጦማሬን።
እዚያም ሂዴሽ በላሽ፣ እዚህም መጥተሽ በላሽ
ሰው ታዘበሽ እንጂ፣ ሆድሽን አልሞላሽ!

Thursday 27 May 2010

ሆ ሆ ይ! ጥጃ ለጅብ?

ወንድሙ መኰንን

“አይሰማ ጆሮ፣ አይውጥ ጉሮሮ” ይሉታል አበው ሲተርቱ። ሌላው የምወደው አባባአል “ጆሮ ምነው አታድግም?” ቢሉት “ይኸን ሁሉ ጉድ እየሰማሁ እንዴት ልደግ?” ብሎ ያለው ነው። አንዳንዴ አንድን አስዳናቂ ነገር በቀጥተኛ አማርኛ ቢሉት አንጀት ስለማያርስ ዘይቤዎች በበለጠ ያብራሩታል። የኢትዮጵያው ጠቅላይ ሥቃይ መለስ፣ ዜናዊ ሕዝቡ በነገር እየጎነተላቸው ሲያስቸግሩአቸው አንዴ ንድድ ብሎአቸው “እኔስ የሰለቸኝ፣ የአማርኛ ተረትና የአፋር ባጄት ነው።” ሲሉ ተደምጠዋል። የአማርኛ ተረትና ምሳሌ እርቃናቸውን ያስቀራቸዋላ!
ወያኔ በመባል የሚታወቀው የዘራፊ ቡድን በሚያስደንቅ አኳኋን የስልጣን ልጓም ከጨበጠ ወዲህ ብዙ ብሔራዊ ጥቅሞችን አሳልፎ እንደሸጠ ጸሐይ የሞቀው ሀቅ ነው፡፡ ገንዘብ ካየ ይኸ የወንበዴዎቹ መንጋ የእናትንም ሬሳ ከመሸጥ የማይመለስ የሼክስፒሩ ሻይሎክ ነው። በረሀ እያለ ያካሄድ የነበረውን ተራ ውንብድና አቶ ገብረመድኅን አርአያ ቁልጭ አድርገው አንድም ሳያስቀሩ እንደመስታወት አሳይተውናል። ኢግላን፣ አሊጤና፣ ባድሜን፣ ጾሮናን፣ ዛላ አንበሳንና መላውን የኢሮብን መሬት እንዳለ ለሌብነት አስተማሪው፣ ለሻዕቢያ በዱቤ እንደቸበቸበው በታላቁ ሴራ መጽሐፋቸው አስተምረውናል። ነገሩ፣ “ማን ይናገር የነበረ፣ ማን ያርዳ የቀበረ” ነዋ! የትግራይ ሕዝብ መሬቴን አላስረክብም ብሎ ባነሳው ግርግር፣ ሌላው ኢትዮጵያዊ ወንድሙ ደርሶለት የደም ዋጋ ከፍሎ ውሉን አፈር ድሜ ቢያስግጠውም፣ መዘዙ እስከዛሬ ድርስ ተምዞ አላልቅ ብሎአል። ኢትዮጵያውያን በደማቸው የተቤዡትን መሬት መለስ ዜናዊ በቅልጥፍናቸው አልጄርስ ድረስ ሂድው አስረክበው መጡ። አባ ግድየልሽን ማን ጠይቆአቸው? የትግራይ ሕዝብ ግን ወይ ፍንክች! ወደፊት ከአቶ ገብረመድኅን አርአያ ጋር አንዳንድ ጉዶችን በሰፊው ልንዳስስ በዕቅድ አሳድረነዋል። ዛሬም ይኸ የወንበዴ ቡድን በተአምር መንግሥት ሆኖም ያንኑ የበረሀ ውንብድብናውን በሰፊው ቀጥሎበታል። ሊትወው ክቶ አልሆነለትም። ሌባ ላመሉ ዳቦ ይልስ የለ! ሲልከሰከስ የተጠናውተው ሰይጣን መቸ በቀላሉ ይለቀውና! ጠብልም እዚህ ላይ ዱልዱም ነው። ዛሬ ወያኔ አገሪቷን ያለ ባሕር በር አስቀርቷታል፡፡ ወልቃይት ጠገዴን ከጎንደር አውጥቶ ወደ ትግራይ ከቶታል። ነገሩ ካንዱ ክፍለ ሀገር መሬት ቆሮሶ ወደሌላው ማሸጋሸግ ይኸን ያህል ባላስመረረን ነበር። ትግራይም የኛ ናት። አገራችን ናት። ግን ትግራይን እንደገንዘቡ ስለሚቆጥራት (ትግሬዎች ኡ! ኡ በሉ! ተዋርዳችኋምል!) ነገ ትርፍ ካገኘ ከመቸበችባት ወደ ኋላ እንደማይል ስለተረዳን ጥሩ ዋጋ እንድታወጣለት አቅዶ ኢያሰባትና እያደለባት መሆኑ ታይቶን ነው እንልፍ የሚነሳን። ጠርጥር! “አለማታለሁ” አለ? “አደልባታለሁ” ቢለን ግልጽ ይሆን ነበር። ከዚያም አልፎ የአጼ ቴዎድሮስን የትውልድ ስፍራ፣ ሁመራንና መተማን ለሱዳን ሽጦታል። በአገሪቱ ያሉትን ለም መሬቶች ለሳውዲ አረቢያ እየቸበቸበ ነው። ትንሺቱ ጅቡቲ ሳትቀር ከዚሁ ወንበዴ አማካይነት ከኢትዮጵያ ከምትገፈው የወደብ ክፍያ መልሳ የኢትዮጵያ መሬት በርካሽ እየገዛች ባለርስት ሁናለች። “ትንሽ ቆሎ ይዘህ ከአሻሮ ተጠጋ” ይሉሀል ይኸ ነው። ሱልጣን ኢብራሂም እብን አህመድ ትንጥዬ ቦታ አሰብ ሰላጤ ውስጥ ለመርከብ ማረፊያ ለሩባቲኖ ኩባንያ (Rubattino company) ሽጦ አልነበር ጣሊያን ኤርትራ የምትባል ቅኝ አገር ለመፍጠር በቅታ ዛሬ ወደብ አልባ ያረገችን? ጂቡቲ ታሪክ ላትደግም ምን ያግዳታል፣ ከሀዲዎች ኢትዮጵያን እስካስተዳድሩአት ድረስ? ዕድሜ ለወያኔ፣ አሁንም የወደብ ጥገኛዋ ሁነናል። አንድ ሰሞን መርካቶ ለአንድ የሩቅ ምሥራቅ ቱጃር ሊቸበቸብ ነበር ሲባል ሰምተን ነበር። ውሉ የት ደረሰ? መርካቶ እስከዛሬ ካልተሸጠች፣ አይቀርላትም። አንድ ቀን ጆሮ ግንዷን ብሏት ኢትዮጵያዊነቷ ተሰርዞ እርፍ ትላታለች።
ወያኔ ገንዘብ ከሸተተው ይሉኝታ አያውቅም። ድሮውንስ ቢሆን ኢትዮጵያዊ ይሉኝታ መቸ ተፈጠረበትና? እንኳ ኢትዮጵያዊ ይሉኝታና ሽታውም ባጠገቡ ዝር ብሎበት አያውቅም። አባሎቹ ሲሰርቁ ቢያዙ “ምን አባክ አገባህ/አገባሽ?” ብለው መልሰው የሚያፈጡ ዓይን አውጣዎች ናቸው። “የሌባ ዓይነ-ደረቅ መልሶ ልብ ያደርቅ” ይሉታል ይኸ አይደል? ወያኔን በአስታውስኩ ቁጥር አንድ የዛሬ 22 ዓመት ገደማ ያጋጠመኝ ሌባ ትዝ ይለኛል። ከጓደኛዬ ጋር ከፕያሳ ስድስት ኪሎ ለመሄድ ታክሲ ልንሳፈር በሩን ስከፍት አንድ ሰው ተንደርድሮ መጥቶ ገፍቶሮኝ ሾፌሩን “ማርካቶ” ይለዋል። መገፋቴ ሲደንቀኝ እጁ የውስጥ ደረቴ ኪስ ገብቶ ሲበረብረኝ አገኘሁት። በደመ-ነፍስ ያዝኩት። በሰውነት ከኔ የማይሽል ነበረና እጁን ከኪሴ ፈልቅቄ አውጥቼው ሳላውቀው በኃይል ጠመዘዝኩት። አቶ ሌቦ ሆዬ በሱው ብሶበርት በጣም ተቆጣኝ። ኩስትር ብሎ ዓይን ዓይኔን እያየ “በቃ ነቅተሀል! ምን ሙዝዝ ትልብኛለህ። ልቀቀኝ! የማነው ሞዛዛ! ፋራ!” ብሎ እንድብራቅ ሲጮኽብኝ ግራ ተገባሁና ያጠፋሁ መስሎኝ ለቀቅኩት። ከመደናገጤ የተነሳ የተተኮሰባት ድኵላ መስልኩ። በኋላ ነገሩ ገርም አለኝና ሳላስበው ሳቄን አወካሁት። እጁን እያሻሸ፣ “ገና ሳምንት ትስቃለህ! ጀዝባ!” ብሎኝ ምንም እፍረት ሳያሳይ እየተጀነነ አንዳንዴም ዞር እያለ እየተገላመጠኝ መንገዱን ቀጠለ። ያ ዓይን አውጣ ሌባና ወያኔዎች አንድ ናቸው። ወያኔዎቹ ባይብሱ! በነገራችን ላይ ወያኔና ዱሩየዎች አብረው እንደሚሠሩ ታውቃላችሁ? እጅና ጓንት ሁነዋል። ሰም ማጥፋት እንዳይመስላችሁ። ዕውነቴን ነው። በሌቦች ተባባሪዎቻቸው አማካኝነት ነበር የፕሮፌሰር አስራትን (ነብሳቸውን በገነት ያኑርልን) ቦርሳ አስነጥቀው በውስጡ የተገኘውን ሰነድ ምንም ሳያፍሩ በጋዜጣቸው ያስወጡት። የጋዜጠኛው ማስታወሻ ደራሲ ተስፋዬ ገብር አብ ይጠየቅ። የኢሰመጉን ቢሮ በዱሩዬዎች አሠብረው ንብረትና ሰነድ እንዳሰረቁ አንድ የኮበለለ የፓሊስ መኰንን ከነመረጃው ለዓለም አጋልጧል።
አገር ቤት ያጧጧፉትን ማጭበርበር ውጭ አገርም ተያይዘውታል። ማጭበርበሪያ ዘዴአቸው በየጊዜው ይለዋወጣል። አንድ ሰሞን በየኤምባሰው የቅጥረኛ ወኪሎቹ አማካይነት ስደተኛውን ሁሉ አዲስ አበባ ውስጥ የከተማ መሬት እንሰጣችሁአለን፣ ኑ ተደራጁ ብለው ልባቸው ውልቅ እስኪል ስበኩአቸው። ይኸን የጠላት ቅጥረኛ ለመታገል ቆርጠን የተነሳን ስደተኞች ወንድሞቻችንና እህቶቻችንን ለማስጠንቀቅ ያደረግነው መሯሯጥ በወያኔ አፍዝ አደንግዝ ድግምት ከሸፈብን። አባሻ ሆዬ ተንጋግቶ ገባለት። የከተማ መሬት በአቋራጭ ተግኝቶ! የወያኔ ባለሟሎች ያንን ሁሉ የስደተኛ አድራሻ ሰብስው፣ “ያውላችሁ፣ ኢትዮጵያውያን ተበደልን ብለው ጥገኝነት ይጠይቃሉ፣ ዳሩ ግን ከአንዳንድ ጽንፈኞች በስተቀር አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ከኛ ጋር ተባብሮ ይሠራል” በማለት የብዙ ሺ ሰዎች ስምና አድራሻ ለየመንግሥታቱ የውጭ ጉዳይ ሚንስትር መሥሪያ ቤቶች አስረክቡ። ለዕውነትኛው ደጋፊአቸው የተወሰኑ መሬቶችን ሰጥተዋቸው፣ የተቀሩትን፣ “ሥጋ የለም መረቅ ጠጡ” ብለው ሸኙአቸው። ያስያዙትም ገንዘብ እንዳለ ውሀ በላው።
ቀጥለው ሁለተኛ ዙር እቅዳቸውን አንድግበው ብቅ አሉ። “ኑ! ንዋያችሁን አገር ቤት አፍስሱ” (investment) ብለው ውጭ አገር ነዋሪ ኢትዮጵያውያንን ጋበዙ። አንዳንዱ አላዋቂ የዋህ አገሩን የረዳ መስሎት፣ “እምን አካባቢ ንዋዬን ላፍሥ (invest) ብሎ ምክር ጥየቃ ገባ። ለዚሁ ጉዳይ የሰለጠኑ ምላሳቸው ጥሬ ይሚቆላ ካድሬዎች መንግሥት የእርሻ መሬት እንደሚሰጣቸውና፣ አበባ ተክሎ ወደ ውጭ መላክ እንደሚያዋጣና ተወዳዳሪ የማይገኝለት የትርፍ ጥገት መሆኑን አሳመኑአቸው። ተደራጁ ተባሉ። ገንዘብ ሰብስቡ ተባሉ። ጅሎቹ እንደተባሉት አደረጉ። ቱጃር የመሆን ሕልማቸው ግን ወያኔ ገንዘባቸውን እኪሱ ከከተተ በኋላ፣ ደብዛው ጠፋ። መሬቱም አልተሰጣቸው፣ አበባውም አላበበ፣ ገንዘባቸውም አልተመለሰላቸው። እዬዬ ቢሉ ማን አዝኖላቸው?
ሶስተኛው ዙር ዕቅዱ በሚሌኒየም ሳቢያ ሚልዩን በሚሊዮን ዶላር ሐይቅ ሊዋኙ የነደፉት ነበር። ከየአንዳንዱ ሚሌኒየም ኢትዮጵያዊ ቱሪስት ቢያንስ ቢያንስ አንዳንድ ሺ ዶላር ሊመነትፉ ተመን አውጡ። የለየላቸው ቁጭ በሉዎች ከሎንዶን ኢምፖርት አደረጉ (ወደ አገር አስገቡ)። ይኽ ዝግጅት የ፲፱፻፺፯ ምርጫን ተከትሎ የጨፈጨፉት የንጹሐን ደም ገና ቀለሙ ከአስፋልቱ ላይ ሳይለቅ ነበር። የቅንጅት መሪዎች “በአገር ክህደት ወንጀል” ተከሰው ወህኒ ታጉረዋል። አንዳንድ ሞኛሞኝ ወገናችን በአፍዝ አድንግዞቹ ድግምት ተታሎ ሊቀላቀላቸው ስንቅ ሲሰንቅ ደርሰንበት፣ ኡ ኡ ብለን ጮኽንበት። “ጥቁር ውሻ ውለድ” ተብሎ ተገጠመበት። አብዛኝው ኡኡታችንን ሰምቶ ጉዞውን ቢሰርዝም፣ ሌሎቹ፣ ገንዘባቸውን ቋጥረው፣ በብዙ ዋጋ የአይሮፕላን ቲኬት ገዝተው “አፍንጫችሁን ላሱ” ብለውን ገቡ። መለስ ዜናዊ ከነሚስታቸው (ውይ ምስኪን!! ሲያሳዝኑ! ኑሮ “ቀዳማይ” እመቤት አዜብ መስፍንን እንደሚያገላታቸው አያችሁ?) በሱዳንኛ ሲደንሱ በቴለቪዢን መስኮት ከማየት በስተቀር ያገኙት አንዳችም ፋይዳ አልነበረም። ለንዶን ላይ ያደረግነው አከባበር እትዮጵያ ውስጥ ከተደረገው ይበልጥ ኢትዮጵያዊ ደርዝ (style) ነበረው።
እኔ የሚገርመኝ፣ የሚታለል ሕዝብ ብዛቱ! ተታሎ! ተታሎ! ተታሎ አለማለቁ! አንዱ ተሞሽልቆ ሲውጣ በብረት ዓይኑ እያየ ሌላው ሊላጭ መግባቱ! ሰሞኑን ጆሮን ጭው ከሚያድረጉት ውስጥ ለውስጥ ከሚሽሎከሎኩት ዓበይት ጉዳዮች መሐል፣ የይሉኝታ ሽታ (DNA) ዝር ያላለበት የዘመናችን ዓይን-አውጣ ቡድን በየትላልቅ የዓለም ከተሞች በወኪሎቹ አማካይነት የሚያደርገው የገንዘብ ፍለጋ መልከስከስ ነው። አሁንስ ብሶበታል። ኢትዮጵያ ውስጥ የሚንቀሳቀሱት የሰብዓዊ መብት ድርጅቶች፣ የሙያ ማኅበራት፣ ተቃዋሚ የፖሊቲካ ድርጅቶች ምንም ዓይነት የገንዘብ ዕርዳታ ከውጭ እንዳይደርሳቸው ሕገ-አራዊት ነድፎ አንቀጽ ቋጥሮ ጥርቅም አድርጎ በሩን ዘግቶባቸዋል። ይኸን ካደረገ በኋላ የራሱን የልመና ኮሮጆ አንጠልጥሎ፣ ያለምንም ሀፍረት በዓለም አቀፍ መንግሥታዊ ድርጅቶች ድጃፍ “ስለ-እመብርሀን” መጽውቱኝ፡ኢያለ ልመናውን በሞኖፖል ተያያዘው። ታዲያ ምን ያረጋል፣ ቢሯሯጥም ቋቱ ጠብ አላለለትም። በሌላ በኩል ደግሞ፣ “አሁን በሌሎች በሩን ሰለጠረቀምኩት፣ ወጭ ያለው ኢትዮጵያዊ ለሎችን መርዳት ስለማይችል፣ ገንዘቡን ለኔ የሚያስረክብበትን ዘዴ ልቀይስ” ብሎ የተነሳ ይመስላል። ጨዋ ለመምሰል መጀመሪያ በዓይጋና በዋልታ የመረጃ ማዛቢያ ድረ-ገጾች ላይ ኢትዮጵያውን “ዶለራችሁን፣ ፓወንዳችሁን፣ የናችሁን እንዳለ በአገራችሁ ባንክ ማስቀመጥ ትችላላችሁ” ብሎ አወጀ። የሰማውም የለ። መልሳችሁ መውሰደም ብትፈልጉ በዚያው ባስቀመጣችሁት አገር ገንዘብ (currency) ይሰጣችሁአል” እያለ ወተወተ። ማን ሰምቶት! እነዚያን ድረ-ገጾች የሚያነብ ኢትዮጵያዊ በቁጥር ኢምንት ነበርና አመርቂ ውጤት አልተገኘም። ለ ዲ ኤል ኤ ፓይፐር በየወሩ 50 ሺ ዶላር ከየት መጥቶ ይከፈል? ጉድ ፈላ። ወያኔ ኤምባሲ ለተለያየ ጉዳይ የሚሄዱትን “ጠቃሚ መረጃ” እያለ ይጠቁማቸው ገባ። አልሆነም። አሁን ግን ነገሩ ዓይኑን አፍጦ መጣ። በታወቁት የወያኔ ቅጥረኛ አውደልዳዮች (ካድሬ) እና ለንዶን ውስጥ ከሚኖሩት፣ እነዚያ ዓባይ ሜዲያ ድረ-ገጽ “ወያኔ! ወያኔ! ወያኔ” እያለ ታርጋቸውን ግምባራቸው ላይ በለጠፈባቸው ሆድ አደር ከርሳሞች አማካይነት ያንኑ ዓይጋ ድረ-ገጽ ላይ ያያችሁትን ፎርም በገፍ እያባዛ በየሬስቶራንቱና በየመሸታ ቤቱ እያስዞረ መከፋፍል ጀምሯል። አልሰሜን ግባ በልው!! ሆ ሆ ይ! ጥጃ ለጅብ አደራ ይሰጣል እንዴ! ገንዘቡን መጣያ ያጣ ኃብታም ካለ ደግ።
እንግዲህ ወያኔ የማጭበርበር መሣሪያውን ወልውሎ በመጣ ቁጥር ከማስጠንቀቅ በሻገር የምናደርገው ነገር አይኖርም። ከዚህ በፊት ተናግረናል። አስጠንቅቀናል። “እምብየው!” ብለው ሂደው ተበሉ። አሁንም ይኸውና አዲስ ዘዴ አንግቦ ሊያጭበረብራችሁ ተነስቷል። አሁንም አዳሜ፣ “እምቢ” ብለሽ ሂደሽ የእሳት ዕራት ከሆንሽ፣ እኛ የምንለው፤ “ወደሽ ከተደፋሽ ቢረግጡሽም አይክፋሽ” ነው። እሰየው ከማለት ባሻገር ከንፈር የሚመጥላችሁ እንደማይኖር ከወዲሁ ዕወቁትና ጥጃችሁን ለጅብ በአደራ ከማስረከብ ታቀቡ።

Saturday 1 May 2010

ቀደዱ እንጂ አልዋሹም!

ከወንድሙ መኰንን

የወያኔ የሹመት ክፍታ የሚለካው በሚዋሽ ምላስ ርዝመት መሆን አለበት። ለዚህ ይሆናል የወያኔ ተሿሚዎች ዓይናቸውን በጨው ሙልጭ አድርገው ታጥበው ሽምጥጥ አድርገው በውሸት እርስ በርስ የሚወዳደሩት። መቸም እራሳቸውን ካልሆነ ማንንም እንደማያሞኙ ግልጽ ነው። በተላይ ዛሬ - ዛሬ ላይ የውሸት ችሎታቸው ኢየታየ መስል ለዲፕሎማሲ ከፍተኛ ሹመት የሚታጩት። ኧረ እባካችሁ ባህልና ጨዋነት ገደል ገብቷል፣ የሕሊና ያለህ!!!!

ከዚህ በፊት፣ ረቡዕ ሐምሌ ፲፩ ቀን ፩፱፻፺፱ ዓ. ም. ወያኔ ወገኖቻችንን ጨፍጭፎ ካበቃ በኋላ የተቃዋሚ መሪዎችን ሰብስቦ እስር ቤት አጉሮ፣ “ሕገ-መንግሥቴን ስላላከበራችሁልኝ፣ እኔን በድምጽ ብልጫ ከዙፋኔ ልታነሱኝ ስለተነሳችሁ ዕድሜ ይፍታችሁ!” ብሎ በሚቆጣጠረው ፍርድ ቤቱ በመፍረዱ የተናደዱ ፲፪ ኢትዮጵያውያን በቀጥታ ገስግሠው የሎንደኑን ኤምባሲ ቁጥጥር ሥር አዋሉት። አንድ ሰዓት ሙሉ ኤምባሲውን ተቆጣጥረው እንግዳ መቀበያ አዳራሹ ውስጥ ያሉት ግድግዳዎች በተጨፈጨፉት ወገኖቻችን ፎቶግራፎች ለጣጥፈው ጥርት ባለ ሰማይ ላይ ርጭት ያሉ ክዋክብት አስመሰሉአቸው። የሚገባውን ሁሉ ተስተናጋጅ ተቀብለው፣ ወያኔ የሚፈጽመውን ወንጀል አንድ በአንድ አስረዱ።

የጀርመን ሬዲዮ በቀጥታ በስልክ ከቦታው ይደረግ የነበርውን ቀድቶ ለሕዝባችን አሰማ። የወያኔ ተላላኪና ጉዳይ አስፈጻሚ ብርሀኑ ከበደ በቦታው አልነበሩም። ሠራተኞቹ ተደናግጠው እንግዳ መቀቢያውን ለተቃዋሚ ሰልፈኞቹ ጥለውላቸው አንደኛው ፎቅ ላይ ዘግተው ፖሊስ ጠሩ። ፖሊስ ደርሶ ወንድሞቻችን ምን እያደረጉ እንደሆነ ጠየቁአቸው። እነሱም አምባሳደሩን ለማነጋገርና ለምን እንዲህ ዓይነት ወንጀል በአገራቸው እንደሚፈጸም ለመጠየቅ መጥተው እንዳጡአቸው አስረዱ። ፖሊሶቹም “በቃ አሁን መልዕክታችሁን በሚገባ ሁኔታ አስረድታችኋል። አሁን ሂዱ” በለው ተማጽነዋቸው ኢትዮጵያውያን ወደየቤታቸው ከአንድ ሰዓት ቆይታ በኋላ አሰናበቱአቸው። ማታ የጀረመን ሬዲዮ ያቀናበረውን አስተላለፈ። የተቃጠለው የሕዝባችን አንጀት ትንሽም ብትሆን በነዚህ ቆራጥ ወገኖች በወሰዱት እርምጃ ራሰ።

ቀጣሪ ጌቶቻቸው ከአዲስ አበባ ደውለው ወረደውባቸው ነው መሰል፣ አባሳደር ብርሀኑ ከበደ ምንም ሳያፍሩ፣ ወደ ጀርመን ሬዲዮ ቢሮ ደውለው “ውሸትን ዕውነት አስመስላችሁ እንዴት ታስተላልፍላችሁ። አንድ ሁለት ቦዘኔዎች ከሕዝቡ ተቅላቅለው እምባሲ ውስጥ ገብተው ነበር። አምስት ደቂቃ ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ተገፍትረው ወጥተዋል። እንዴት ያንን ወሬ ብላችሁ ታወራላችሁ ብለው” አምባረቁቸው። የጀረመን ሬዲዮም ዕድሉን ሰጥቶአቸው በሚቀጥለው ቀን ውሸታቸውን እንዲቀዱት ፈቀደላቸው። መቸም ጆር አይሰማ በዚህ ዕድሜአቸው ሲቀዱ ሰማንላቸው። “ስጥ እንግዲህ!” ይላል አራዳ ልጅ። ይኸ ጸሐፊ ወንድሞቻችን ኤምባሲውን ከተቆጣጠሩት ሰዓት ጀምሮ እስከለቀቁ ደረስ ሁኔታውን ይከታትል ነበር። ልጆቹ የሠሩት ጅግንነት ከምንም በላይ ሊዘገብ ቢችልም ዝም ብሎ አልፎት ነበር። የአምባሳደሩን ቀደዳ ከሰማ በኋላ ግን “የምጣዱ እያለ የዕንቅቡ ተንጣጣ” በሚል ርዕስ በዕውነት የሆነውን በቪዲዮ “መቅረጸ-ስዕል” ተጨባጭ መረጃ አሰደግፎ አምባሳደር ተብዬው ያሉት በሙሉ ውሸት መሆኑና ሂሊናቸውን ሽጠው የሆነውን አልሆንም እንዳሉ አስቀመጠላቸው። ጽሑፍ አንብበው፣ ቪዲዮውን አይተው ካበቁ በኋላ አምባሳደር ሆዬ እዬዬአቸውን አቀለጡት። ሎንዶን ሜትሮፖሊታን ፖሊስ ጣቢያ ሩጠው ሂደው “እሪ አለቅን! ሕግ ባለበት አገር ሕገ-ወጥ ቦዜኔዎች በጉልበት ኤምባሲአችንን ያን ሁሉ ሰዓት ሲቆጣጠሩት አንድ ሰው እንኳን እንዴት አላሰራችሁም። የዲፕሎማቲክ ጥበቃችሁ ተጓደለብን፣ የኢትዮጵያና የእንግልዝ ወዳጅነት በዚሁ ጉዳይ ሊያከትም ነው። አንድ ነገር አድርጉ። ይኸው ከአንድ ሰዓት በላይ በሰላም ለመሥራት ዋስትና የለንም። ዛሬ ያለምንም ችግር ኤምባሲውን ተቆጣጥረውት ከሄዱ ነገ መጥ|ተው ላይገድሉን ምን ዋስትና አለን ... “ ገለመሌ አሉ!! “ቪዲዮውን እዩት!! አልቀናል! እንዴት ዝም ትላላችሁ!” በማለት በዚያው በጀርመን ሬዲዮ “ሁለት ሰዎች፣ አምስት ደቂቃ” ባሏት አፋቸው መልሰው ፖሎሶች ላይ አለቀሱባቸው። ፖሊሶቹም ይሄንን ድርገት መርቷል ያሉትን አንዱን ወንድም ጠርተው፣ የውያኔውን አምባሳደር ዕንባ ለመጥረግ ያህል፣ አስጠነቀቁት።

የወያኔው ተላላኪ፣ አምባሳደር “ብርሀኑ ከበደ” ከዚያ ትምህርት ወስደው “ሳይገድሉ ጎፈሬ፣ ሳያረጋግጡ ወሬ” እንደማይደግማቸው ተስፋ አድርገን ነበር። ዳሩ ምን ያደርጋል አሁንም ደገሙት። ያሁኑ ይባስ!!! ያሁኑ ይባስ!!! ወይ ቅሌት!!

ሰኔ ፱ ቀን ፪ሺ፩ ዓ. ም. ኢትዮጵያውያን የወያኔ መንግሥት የሚያደርሰውን ጭፍጨፋ፣ ጠቅላላ የሰባዓዊ መብት ገፈፋ፣ እና ዓይን ያወጣ ንቅዘት ወይም ሙስና፣ ብርቲሽ የተመራጮች ምክር ቤት አባላት፣ ለበጎ አድራጎት ድርጅት አባላት፣ ለትብብር ከውሦስተኛው ዓልም ሕዝብ ጋር (Solidarity with the Third World) አባላት እና ለጋዜጠኞች ሶስት ሰዓት የፈጀ ገለጻ በሀውስ ኦፍ ኮመንስ በሚባለው የተመራጮች ምክር ቤት (House of Commons) አቅረበው ነበር። ገለጻው የብዙዎችን ዓይን የከፈተ እና ብዙዎቹ ጉድ ያሉበት ነበር። ይኸንን ከፍተኛ ስብሰባ በዓይነቱ ልዩና የመጀመሪያው በመሆኑ፣ አዘጋጆቹን ቪኦኤ በመባል የሚታውቀው የአሜሪካን ድምጽ ሬድዮ እና የጀርመን ሬዲዮ አዘጋጆቹን አፈላልገው ቃለ መጠይቅ (interview) አድርገው ነበር። ይኸ ሁኔታ ውያኔን ከምንም በላይ አስደነገጠው። የሚይዙትን የሚጨብጡትን ያጡት ለማጁ የወያኔ ተላላኪ ቦቦታው ሳይኖሩ፣ ለአሜሪካን ድምጽ ሬዲዮ ዓይን ያወጣ የውሸት ስልቻቸውን እንደገና ደገሞው ቀደዱት።

“በመጀመሪያ ደረጃ፣ እንዲህ ዓይነት ስብሰባ አልነበረም፣ የነበረው ትብብር ከሶስተኛው ዓልም ሕዝብ ጋር (Solidarity with the Third World) በቅርቡ ገንዘብ ለማሰባሰብ ያደረገው ቅደመ ስብስብ ነበር። አንዲት ሳብራ የምትባል ሴት እነዚህ ተቃዋሚ ነን የሚሉ ሰዎች በጎን ጠራርታ አመቻችታላቸው ነው የገቡት”

በማለት አጥላልተው፣ አወዳድቀውና አቃለው ለማለፍ ሞክረው ነበር። ጋዜጠኛው “እንደስዚህ ዓይነት ስብሰባ አልተደረገም ነው የሚሉኝ?”ብሎ ሲያፋጥጣቸው፣
“አይ አልተደረገም አላልኩም። የኢትዮጵያን ጉዳይ ለመነጋገር የተጠራ ስብሰባ አልነበረም። እኛ አልተጋብዝንም። ስብሰባው ተደርጓል ግን በትንሽ ክፍል 14 ቁጥር ውስጥ የተደረገ አነስተኛ ስብስባ ነበር። አንድም የፓርላማ አባል አልነበረም”

በማለት ዘባርቀዋል። ውሸታቸው ያሳፈረው ጋዜጠኛ አዲሱ አበበም ግርም ብሎት፣ “የተከበሩ ብሩስ ጆርጅ አልነበሩም ነው የሚሉኝ” ሲላቸው፣ ድንግጥ ብለው “አይ ለትንሽ ደቂቃዎች ነበሩ። ትንሽ ካዳመጡ በኋል ውልቅ ብለው ወጥተዋል” በማለት ሽምጥጥ አድረገው ሳያፍሩ ክደዋል። “አይነጋ መስሏት” ነው አበው የሚሉት?

በመጄሪያ ደረጃ፣ ስብሰባው የተደረገው፣ ኢትዮጵያው ውስጥ ለሚደረገው አፈናና ጭቆና ለአገሪቱ ፓርላማ፣ በጎ አድራጎት ድረጅቶች፣ ሰብዓዊ መብት ድርጅቶች፣ ትብብር ከሦስተኛው ሕዝብ ጋር እና ለጋዜጠኞች ታስቦ የተደረገ እንጂ ለገንዘብ ማሰባሰቢያ ቅደመ ዝግጅት አልነበረም። “ወሸት ቁጥር አንድ” በሉ! ፲፬ ቁጥር ክፍል አነስተኛ በመሆኑና የሚመጡት እንግዶች ከሦስት መቶ በላይ በመሆናቸው፣ ከዚያ ባሻገር ወያኔ የፈጸማቸው የዘር ማጥፋት ቪዲዮና በሙስና የተዘፈቀበት መረጃ በፕሮጀክተር ስለሚቀርብ ስብሰባው የተደረገው በታላቁ የኪሚቲ ስብሰባ አዳራሽል (The Grand Committee Room) ነበር። ውሸት ቁጥር ሁለት በሉ። አንድም የፓርላማ አባል የለም ብለው ዓይናቸውን በጨው አጥበው ለሸመጠጡት፣ ጉባዔውን የከፍቱት በክብር እንግድነት የሁሉም ፓርቲዎች የምክር ቤት ሊቀመንበር፣ የተከበሩ ዴቪድ አንደርሰን (The Chairman of All Party Parliamentary Group on Third World Solidarity, MP David Anderson) ነበሩ። ውሸት ቁጥር ሦስት በሉ! አምባሳደር ተቢዬው ሲወጠሩ ተውናብደው አንደርሰን ብቻ ተገኝተው ነበር። ውሸት ቁጥር አራት! አንደርሰን ብቻ አለነበሩም። ከመኖርም አልፈው የመዝጊያ ንግግር ያደረጉት የተከበሩ ብሩስ ጆርጅ ነበሩ። ውሸት ቁጥር አምስት። አንድም ጋዜጠኛ አልነበርም ላሉት፣ “ተመክሮና የአሁኑ የሜዲያ ሽፋን በኢትዮጵያ (Exeprience and The Current Media Coverage in Ethiopia) በሚል ርዕስ ንግግር ያደረገችው ታዋቂዋ የጋርዲያን (The Guardian) ጋዜጣ ዘጋቢ ሳውንድራ ሳተርሊ (Saundra Satterlee) ነበረች። ውሸት ቁጥር ስድስት! በስንት ፍጥጫ የተከበሩ ብሩስ ጆርጅን መገኘት ያመኑት አማሳደር ብርሀኑ (ምኑን ብርሀን ሆኑ)፣ ብሩስ ጆርጅ አቋርጠው ሂደዋል ላሉት፣ የመዝጊያ ንግግራቸውን ሲያደርጉ፣ “If there were a contest in the severity of corruption the rulers of Ethiopia, who have redefined the word, would undoubtedly win the gold prize.” (በሙስና ዝቅጠት ውድድር ቢደረግ፣ የቃሉን አዲስ ፍቺ ያገኙልን የኢትዮጵያ መንግሥት መሪዎች፣ የወርቅ ሜዳሊያ አሸናፊ ሁነው ባጠለቁ ነበር) በማለት ተሰብሳቢውን አስቀውታል። ከዚያም አልፈው ተርፈው በመጨረሻ የዚህን ጽሑፍ አቅራቢ ውጪ ጠብቀው ወደ ጎን ወስደውት አንዳንድ ነገሮቻን ካወያዩት በኋላ ወደፊት ተገናኝተው በሰፊው መረጃ መሰብሰብ ላይ አብረው ለመሥራት ወስነዋል።

ተወካይ አልላኩም ላልቱ ጭልጥ ላለ ቅጥፈት፣ በመጀመሪያ ደረጃ እሳቸው በቦታው አልነበሩም፣ ታዲያ ማን መረጃውን አጥናቀረላቸው? እልፍኝ አስክልካያቸው ሆድ-አደር ያለው ከበድ እዚያ ጉጉት መስሎ ጉልት ብሎ አላመሸም? እንዲያውም አይታው ብግን ያለች አንድኛዋ እህታችን፣ “እምባሲ በር ይዞ አትገቡም እያለ ዘበኛ ይመስል ፍርፋሪ ለቃሚ የወያኔ እልፍኝ አስከልካይ ምንድነኝ ብሎ ነው እዚህ የተጎለተው? ወይ አያምር ወይ አያፍር!” ብላ የዚህን ጽሑፍ አቅራቢ አስቃዋለች። ያስ ሌላው ተላላኪአቸው? ዓለማየሁ ነኝ ያለው (ዓለሙ ጥፍት ትበልበትና)! አንዷ እህታችን “ዶማ” ያለችው! ስለወያኔ ሙስና በቀረበው በዚያው መድርክ፣ “ይኸ መንግሥት ብዙ ለውጥ አምጥቷል። ብዙ ወጣቶችን ባለመኪና አድርጓል” ብሎ ሲናገር ሕዝቡስ ጮሆበት አፉን አላስዘጋውም? ሚዛናዊ አይደላችሁም ብሎ ለመናገር ሲሞክር፣ አንዳዶቹ በጣም ከመናደዳቸው የተነሳ “የት ያለህ መሰለህ? የኢትዮጵያ ፓርላማ?” እያሉ ይጮኹብት የማን መልዕክተኛ ነበር?

በቦታው የነበሩ አንድ የቀድሞ የዲፕሎማቲክ ከፍተኛ ባለሥልጣን የቪኦኤውን ትርተራ እንዳዳመጡ፣ ለዚህ ጽሑፍ አቅራቢ ደውለው፣
“ብርሀኑ ከበደ፣ የዲፕሎማሲን ሙያ አዋረደ። ሁላችንም ድፕሎማት ነበርን። የአገርን ጥቅም ለማስከበር የስብዕናን ክብር ሳያዋርዱ መሥራት ምንም ነውር የለበትም። ግን እንዲዚህ መቀደድ ያሳፍራል። ቤልጀይም ጁኒየር ድፕሎማት ሁኖ ሲሠራ ደህና ወጣትና ወደፊት ጥሩ ባለሟል ይኾናል ብዬ ስጥብቅ ነበር። እንዲህ ዓይነት ወራዳ ሥራ ሲሠራ በማየቴ አዘንኩ”
ብለዋል።

አምባሳደር ብርሀኑ ከበደ፣ ቤልጀየም በነበሩብት ጊዜ የደርግ ጥቅም አስጠባቂ ነበሩ። እሱስ ይኹን፣ ያን ጊዜ የደርግን መንግሥት ያገለግሉ የነበሩ፣ ሥርዓቱ ሲወድቅ፣ መጪው መንግሥት አገር ጎጂ በመሆኑ እንዳለ ተሰደዋል። ክፍተት ሲገኝላቸው ሰልፋቸውን አስተካክለው አምባሳደር ተባሉ፣ ያውም የወያኔ! አምባሳደር ብርሀኑ! ሞኝ አይሁኑ! ትንሽ እንኳን የኢትዮጵያ ሕዝብ ይቅር እንዲልዎት እንዲህ ዓይነቱን የወራዳ ሥራ እራስዎ አይስሩ። የሕዝብ ግንኙነት ክፍል ኃላፊ የለዎትም? እሱ ወጥቶ ይቀላምድ። እርስዎ ምን በወጣዎት! እንዲይ ዓይነቱን መቅደድ ለቦታው የተዘጋጀ ሰው ይቀደደው። ልብ ይበሉ። ይኸ ምክር የወዳጅ ምክር ነው። ይልቅ እስዎ ወያኔ አይታመንም እና ልክ እንደ ፍሰሀ አዱኛ በጊዜ ሹልክ ብለው ያምልጡ። ይሻልዎታል። ለምን ቢሉኝ፣ ጌታዎ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሥቃይ፣ መለስ ዜናዊ ብለው ጨርሰውታል። ጠቅላይ ሥቅዩ ምን አሉ መሰሰዎት!

“የወያኔ ሹመት የዛፍ ላይ እንቅልፍ ነው። ሽልብ ካሉ ዱብ ነው።”

ማንም አምባ ገነን መንግሥት ሥልጣንን ሙጭጭ ብሎ ለዘልዓለም ጨብጦ የኖረበት ታሪክ በአገራችንም ሆነ በሌላው ዓለም ታይቶ አይታወቅም። ሁሉም አምባገነን ሌሎቹን እንዳዋረደ እሱም በተራው ተዋርዶ ከሥልጣን ይወርዳታል። አብዛኛው የአምባገነን ከነግሳንግሱ ለሌሎች ባዘጋጃት ወጥመድ እራሱ ይገባባታል። ከቀናውም ለስደት ይዳረጋል። እንደርስዎ ላሉት ለጀሌዎቹ ወይውላቸው። ወያኔ የኢትዮጵያውያንን ቆሽት አሳርሮ አይኖራትም። አምባሳደር ብርሀኑ! በሰፈርዎ የዕውነት ብርሀን ደብዛዋ እንደ አዲስ አበባው መብራት ጠፍታለች። አሁንስ ጨለማው ከበደ።